ባህር ዳር ፣ ሚያዚያ 14 / 2018 (የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍ/ቤት)
በካቶሊክ የበጎ አድረጎት አገልግሎት የኢትዮጵያ ተወካይ የሆኑት አቶ ዘመዴ ዘውዴ ዛሬ ሚያዚያ 14 ቀን 2018 ዓ.ም በባህር ዳር ከተማ ተገኝተው በአማራ ክልል ጠቅላይ ፍ/ቤት የሥራ ጉብኝት አድርገዋል።
አቶ ዘመዴ ከጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዘዳንት ክቡር አቶ አለምአንተ አግደው ጋር ተገናኝተውም በቀጣይ በጋራ በሚሰሩ ጉዳዮች ላይ የሁለትዮሽ ዉይይት አድርገዋል።
ፍ/ቤቱ የጀመረው የለውጥ ሥራ አካል የሆኑ የስማርት ኮርት፣ የኢ- ፋይሊንግ፣ ዲጅታል የአንድ ማዕከል የዳኝነት አገልግሎት እና ሌሎች የለውጥ ሥራዎችን የጎበኙ ሲሆን፣ ፍ/ቤቱ የጀመራቸው ዘርፈ ብዙ የለውጥ ሥራዎችን አስመልክቶ በአቶ አለምአንተ ገለፃ ተደርጎላቸዋል።
አቶ ዘመዴ በበኩላቸው፣ ፍ/ቤቱ የጀመራቸው የለውጥ ሥራዎች አስደሳች መሆናቸውን እና ከጠቅላይ ፍ/ቤቱ ጋር አብሮ ለመስራት የሚቻልባቸውን ሁሉንም አማራጮች እንደሚያዩ ገልፀው፣ በጠቅላይ ፍ/ቤቱ የተመዘገበው የለውጥ ሥራ ውጤት በፍትህ ስርዓቱ ውስጥ ሞዴል ሊሆን የሚችል እና በሁሉም አካባቢዎች ሊሰፋ የሚገባው ነው ብለዋል።
